የአፍሪካን የክትባት እና የሕክምና ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ያለመው ግዙፉ "ACHIEVE Africa" የተሰኘ ኢኒሼቲቭ ከ39ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ጎን ለጎን በይፋ ተመሠርቷል
በኢኒሼቲቩ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ላይ የተገኙት የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህብረት እ.ኤ.አ በ2040 የክትባት ፍላጎትን 60 በመቶ በአህጉር ውስጥ ለማሟላት ያስቀመጠውን ግብ ለማሳካት ግንባር ቀደም ሚና እየተጫወተች መሆኑን የገለጹ ሲሆን መንግስት የመድኃኒት ግዥ ስርዓቱን በአገር ውስጥ ለሚመረቱ ምርቶች ቅድሚያ እንዲሰጥ በማሻሻሉ፣ በዘርፉ የአገር ውስጥ ፍላጎትን ሽፋን ከ8 በመቶ ወደ 42 በመቶ ማደጉን ጠቁመው በቀጣይ አምስት ዓመታት ወደ 60 በመቶ ለማሳደግ ታቅዶ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም አረጋግጠዋል።
\
ኢትዮጵያን የፈጠራ ማዕከል (Innovation Hub) ለማድረግ ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን የገለጹት ዶ/ር መቅደስ የሀገሪቱ የክትባት የማምረት ጉዞ አሁን ላይ "ይሳካል ወይ?" የሚለው ጥያቄ ቀርቶ "እንዴት እና በምን ፍጥነት?" ወደሚለው ወሳኝ ምዕራፍ መሸጋገሩን አስታውሰዋል።